የቴክኖሎጂና የክህሎት ውድድሩ የንድፈ ሀሳብ እውቀቶችን ወደ ተግባር ለመለወጥ ያግዛል - የውድድሩ ተሳታፊዎች - ኢዜአ አማርኛ
የቴክኖሎጂና የክህሎት ውድድሩ የንድፈ ሀሳብ እውቀቶችን ወደ ተግባር ለመለወጥ ያግዛል - የውድድሩ ተሳታፊዎች

ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዚያ 15/2017(ኢዜአ)፦ ክልል አቀፍ የቴክኖሎጂ፣ የክህሎት እና የተግባራዊ ጥናትና ምርምር ውድድር በንድፈ ሀሳብ ያገኙትን እውቀት ወደ ተግባር ለመቀየር እንደሚያግዛቸው የውድድሩ ተሳታፊዎች ገለጹ።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ቢሮ "ብሩህ አዕምሮዎች በክህሎት የበቁ ዜጎች" በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጀው ክልል አቀፍ የቴክኖሎጂ፣ የክህሎትና የተግባራዊ ጥናትና ምርምር ውድድር በወላይታ ሶዶ እና በአርባ ምንጭ ከተሞች እየተካሄደ ነው።
በወላይታ ሶዶ ከተማ በተጀመረው ውድድር ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የውድድሩ ተሳታፊዎች እንደገለጹት የውድድሩ መዘጋጀት በኮሌጆች ያገኙትን የንድፈ ሀሳብ ዕውቀት ወደ ተግባር ለመቀየርና ልምድ በማዳበር የበለጠ ለመስራት የሚያግዛቸው ነው።
በቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች የሚሰጡ ስልጠናዎች ከቴክኖሎጂ ጋር በመላመድና ምርታማ በመሆን የኢኮኖሚና ማህበራዊ ችግሮቻችን በራስ አቅም መፍታት የሚያስችሉ መሆናቸውንም ነው የተናገሩት።
ከሳውላ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የአትክልትና ፍራፍሬ ማቀነባበሪያ ቴክኖሎጂ የፈጠራ ውጤትን ይዞ የቀረበው ተወዳዳሪ ተመስገን አዝማች ክልላዊ ውድድር መዘጋጀቱ በኮሌጅ ያገኘነውን የንድፈ ሀሳብ ዕውቀት ወደ ተግባር በመቀየር ይበልጥ ተጠቃሚ እንድንሆን ያስችለናል ብሏል።
በቴክኖሎጂ በመታገዝ ተኪ ምርቶችን በስፋት በማምረት የህብረተሰቡን ፍላጎት ለማሟላት ትልቅ መነሳሳት የሚፈጥር መሆኑንም ነው የተናገረው።
ውድድሩ ከጠባቂነት አስተሳሰብ ወጥቶ በራስ ጥረት ሠርቶ ለመለወጥ የሚያነሳሳ ነው ያለችው ደግሞ ከዲላ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በምግብ አዘገጃጀት ክህሎት የተወዳደረችው ፍጹም ዮሐንስ ናት።
ውድድሩ ልምድ በመለዋወጥና ክፍተቶቻችንን በማረም በቀጣይ ምርታማ ለመሆን ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብላለች።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ቢሮ ምክትልና የቴክኖሎጂ ሽግግርና ኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን ዘርፍ ሃላፊ አቶ በዛብህ ገበየሁ በበኩላቸው እንዳሉት የውድድሩ መዘጋጀት ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመተካት እየተደረገ ያለውን ጥረት የሚያግዝ ነው።
በቢሮው ስር ባሉ ኮሌጆች የሚሰጠው ተግባር ተኮር ትምህርትና ስልጠና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሚተኩ ቴክኖሎጂዎች ላይ ትኩረት ያደረገ መሆኑንም አመልክተዋል።
ከቴክኖሎጂ ማዕከላት የፈጠራ ሀሳቦችንና ቴክኖሎጂዎችን በመሰብሰብ ሰልጣኞች ስልጠናቸውን ሲጨርሱ በተናጠልም ሆነ በጋራ ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመው ውጤታማ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
ቴክኖሎጂዎችና የፈጠራ ሀሳቦች የማህበረሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግሮች በመሰረታዊነት እንዲፈቱ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱንም ነው የገለጹት።
ለአራት ቀናት በሚካሄደው ክልል አቀፍ ውድድር በክህሎት ዘርፍ በ20 ሙያዎች፣ በቴክኖሎጂ ዘርፍ ደግሞ በ14 ቴክኖሎጂዎች እንዲሁም በ6 ተግባራዊ ጥናትና ምርምር ሥራዎች ውድድሩ እንደሚካሄድ ታውቋል።
በውድድሩ የተለያዩ አሰልጣኝ መምህራን፣ ሰልጣኞችና ኢንተርፕራይዞች በመሳተፍ ላይ ናቸው።