የአሜሪካው ኩባንያ በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የሃዋላ አገልግሎትን የማስፋት ፍላጎት እንዳለው ገለጸ - ኢዜአ አማርኛ
የአሜሪካው ኩባንያ በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የሃዋላ አገልግሎትን የማስፋት ፍላጎት እንዳለው ገለጸ

አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 17/2017 (ኢዜአ)፡-የአሜሪካው ቪዛ ባንክ ኩባንያ ኢትዮጵያን ጨምሮ በቀጣናው ዓለም አቀፍ የሃዋላ አገልግሎትን የማስፋት ፍላጎት እንዳለው አስታወቀ።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከአሜሪካው ቪዛ ኢንክ ዓለም አቀፍ የክፍያ ካርድ አገልግሎት ኩባንያ ጋር በሃዋላ፣ በዲጂታል ፋይናንስና በአዳዲስ የትብብር ዕድሎች ላይ በጋራ ለመስራት መክረዋል።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሹሩን ዓለማየሁ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ መንግስት በእኩልነትና በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ የዲጂታላይዜሽን ትብብር እንዲጎለብት ከፍተኛ ፍላጎት እንዳለው ገልጸዋል።
የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስኬት ለማረጋገጥ በህግ ማዕቀፍ፣ በመሠረተ ልማቶችና በሰው ኃይል ግንባታ ላይ ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል።
ሀገራዊ ስራዎችን ዲጂታላይዝ ለማድረግና የፋይናንስ ምርቶችንና አዳዲስ አገልግሎቶችን በኢትዮጵያ ለማዳረስ ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል።
የቪዛ ኢንክ የደቡብና ምስራቅ አፍሪካ ሪጅን ምክትል ፕሬዝዳንት ሚካኤል በርነር ዓለም አቀፍ የቪዛ አገልግሎትን በኢትዮጵያ እና በቀጣናው ሀገራት ተደራሽ ለማድረግ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው ገልፀዋል።
የቪዛ ክፍያ የዲጂታል ስነ-ምህዳርን በኢትዮጵያ ለማጎልበት እንደሚያስችል ጠቁመው፥ ዓለም አቀፍ እና ክልላዊ ምርጥ ተሞክሮዎችን ተግባራዊ እንደሚደረግ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያን አጠቃላይ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን አጀንዳ እንዲሁም የዲጂታል ስትራቴጂ ፕሮጀክቶች እና የትግበራ እቅዶችን አስመልክቶ በጋራ ለመስራት ስምምነት ላይ መደረሱን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመለክታል።